ክፍለ ጊዜ 1
መግባት
(1 min)
ሁሉንም ተሳታፊዎችና አስተባባሪዎች እንዲገቡ አድርጉ።
Or six.zume.training/checkin and use code: 3354
ፀልዩ
(5 min)
በጸሎት ጀምሩ። ያለ መንፈስ ቅዱስ መንፈሳዊ ማስተዋል ማግኘትና መለወጥ አይቻልም። በዚህ ክፍለ ጊዜ ወቅት እንደ ቡድን መንፈስ ቅዱስን ለመጋበዝ ጊዜ ውሰዱ።
ማጠቃለያ
(1 min)
በዚህ ክፍለ ጊዜ፣ እነዚህን ጽንሰ-ሐሳቦች እንሰማለን እና እንነጋገራለን፡-
- እግዚአብሔር ተራ ሰዎችን ይጠቀማል
- የደቀ መዝሙር እና የቤተክርስቲያን ቀለል ያለ ፍቺ
- መንፈሳዊ መተንፈስ እግዚአብሔርን መስማት እና መታዘዝ ነው።
READ
(5 min)
እግዚአብሔር ተራ ሰዎችን ይጠቀማል
ወደ ዙሜ ሥልጠና እንኳን በደህና መጣችሁ! ዙሜ(Zume) የግሪክ ቃል ሲሆን ትርጉሙም "እርሾ" ማለት ነው፡፡ ኢየሱስ እንዳለው የእግዚአብሔር መንግሥት ጥቂት "እርሾ" ወስዳ ብዙ ሊጥ ውስጥ የከተተችን ሴት ትመስላለች፡፡ ሴት የዋ እርሾውን በሊጡ ውስጥ ስታኖረውም፣ እርሾው ሊጡን ሁሉ እስኪያቦካው ድረስ ይስፋፋል፡፡ በዚህም ንግግሩ ኢየሱስ ያስረዳው አንድ ተራ ሰው በጣም ትንሽ ነገር ወስዶ ታላቅ ተጽዕኖ ፈጣሪ የሆነን ነገር ለመፍጠር ሊጠቀምበት እንደሚችል ነው! ሕልማችን ኢየሱስ ያለውን ለማድረግ ነው… በዓለም ሁሉ ያሉ "ተራ" የሚባሉ ሰዎች ታናናሽ መሣሪያዎችን ወስደው በእግዚአብሔር መንግሥት ውስጥ ታላቅ ተጽዕኖ እንዲፈጥሩ መርዳት! ኢየሱስ ለተከታዮቹ በመጨረሻ ጊዜ የሰጣቸው ትዕዛዝ ለመረዳት ቀላል ነበሩ፡፡ እንዲህ ነው ያላቸው፡- "ሥልጣን ሁሉ በሰማይ እና በምድር ተሰጠኝ፡፡ እንግዲህ ሂዱና አሕዛብን ሁሉ በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችኋቸው፥ ያዘዝኋችሁንም ሁሉ እንዲጠብቁ እያስተማራችኋቸው ደቀ መዛሙርት አድርጓቸው፤ እነሆም እኔ እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ ሁልጊዜ ከእናንተ ጋር ነኝ።" የኢየሱስ ትዕዛዝ ቀላል ነው፤ "ደቀ መዛሙርት አድርጉ" የሚል ነው፡፡ ትዕዛዙን እንዴት እንደሚፈጽሙም የነገራቸው ነገር ቀላል ነው፤ በምትሄዱበት ሁሉ ደቀ መዛሙርትን አድርጉ፡- በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችሁ ያዘዘውን ሁሉ እንዲያከብሩ እነርሱን በማስተማር ደቀ መዛሙርት አድርጉ፤ ሆኖም አንድን ሰው ደቀ መዝሙር ማድረግ ምን ምን ደረጃዎች አሉት? 1 - ደቀ መዛሙርት ማድረግ ያለብን ሁልጊዜ ነው፤ የትም ብንሄድ፤ 2 - አንድ ሰው ኢየሱስን ለመከተል ሲወስን - መጠመቅ አለበት፡፡ 3 - አንድ ሰው ኢየሱስን በመከተል እያደገ ሲሄድ፣ ኢየሱስ ያዘዘውን ሁሉ እንዴት መታዘዝ እንዳለበት ማስተማር ይገባል፡፡ ኢየሱስ ካዘዛቸው ነገሮች አንዱ ደቀ መዝሙር ማድረግ እንደመሆኑ፣ ኢየሱስን የሚከተል ሁሉ ሰዎችን እንዴት ደቀ መዝሙር ማድረግ እንዳለበት መማር አለበት፡፡ ደቀ መዛሙርት ደቀ መዛሙርትን ማፍራት አለባቸው፡፡ እነዚያ ደቀ መዛሙርት የሆኑትም ደቀ መዛሙርትን ማፍራት አለባቸው፡፡ ደቀ መዛሙርትን ማብዛት አለባቸው፡፡ ዙሜ የሚሠራውም እንደዚህ ነው፡፡ ልክ እንደ እርሾ ነው፤ ሊጡ ሁሉ እስኪቦካ ድረስ በሊጡ ውስጥ ይሠራል፡፡ ኢየሱስ ደቀ መዛሙርቱ ደቀ መዛሙርትን እንዲፈሩ ሲያዛቸው፣ አንድ የተስፋ ቃል ሰጥቷቸዋል፤ "እነሆ እኔ እስከ ዓለም ፍጻሜ ሁልጊዜ ከእናንተ ጋር ነኝ" ብሏቸዋል፡፡ የኢየሱስ ተከታይ ሁሉ ታዲያ እርሱ ሁልጊዜ ከእኛ ጋር የመሆኑን ነገር ሊያስበው ይገባል፡፡ ምክንያቱም ኢየሱስ እንዳለው ከእኛ ጋር ስለሆነ! ይህም ማለት የእርሱ ተከታይ የሆንን እኛ እያንዳንዳችን ደቀ መዛሙርትን እንድናፈራ ለሚፈልገው ለኢየሱስ ራሳችንን ማስገዛት አለብን ማለት ነው፡፡ እርሱ ከእኛ የሚፈልገው ይህንን ነው፡፡ ኢየሱስ እንዲህ ብሏል፡- "… ሥልጣን ሁሉ በሰማይና በምድር ተሰጠኝ። እንግዲህ ሂዱና አሕዛብን ሁሉ... ደቀ መዛሙርት አድርጓቸው፤" እኛን የላከን ኢየሱስ የተደገፈበት ሥልጣን … የራሱ ሥልጣን ነው፡፡ እርሱ እንዳለውም ከዚህ የሚበልጥ ሥልጣን የለም፡፡ ከእርሱም የሚበልጥ ሥልጣን ያለው ትውፊት የለም፡፡ ከዚህ የሚበልጥ ሥልጣን ያለው ባህልም የለም፡፡ ከዚህ የሚበልጥ ሥልጣን ያለው ሕግም በምድር ላይ አልታየም፡፡ ኢየሱስ ያለው ይህንን ነው፡- "ሂዱና ደቀ መዛሙርት አድርጉ፡፡" ሥራው ሁሉ ተሠርቶ እስኪያልቅ ድረስ፣ ልክ እንደ ዙሜ - ልክ እንደ እርሾ - መሄዳችንን እና ማደጋችንን እንቀጥላለን፡፡
ተወያዩ
(10 min)
- ኢየሱስ ሁሉም ተከታዮቹ ለታላቁ ተልዕኮ እንዲታዘዙ ካሰበ፣ ለምንድነው ጥቂቶቹ ብቻ ደቀ መዛሙርት የሚያደርጉት?
READ
(5 min)
ደቀ መዛሙርት እና ቤተ ክርስቲያን
እንኳን ወደ ዙሜ ሥልጠና እንደገና በሰላም መጣችሁ፡፡ በዚህ ክፍለ - ጊዜ ስለደቀ መዛሙርት እና ስለቤተ ክርስቲያን እንነጋገራለን፡፡
ደቀ መዝሙር ምንድነው? ሰውን ደቀ መዝሙር የምታደርጉትስ እንዴት ነው?
አንድን የኢየሱስ ተከታይ የሆነን ሰው የእርሱን ትዕዛዛት ሁሉ እንዲታዘዝ የምታስተምሩት እንዴት ነው?
እንደ ዓለም እሥረኛ ይኖር የነበረን አንድን ሰው የእግዚአብሔር መንግሥት ዜጋ አድርጋችሁ የምታስታጥቁት እንዴት ነው?
ደቀ መዝሙር የሚለው ቃል ትርጉሙ ተከታይ ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ደቀ መዝሙር የእግዚአብሔር ተከታይ ነው፡፡
"ኢየሱስም ቀረበና እንዲህ ብሎ ተናገራቸው፦ ሥልጣን ሁሉ በሰማይና በምድር ተሰጠኝ።"
ስለዚህ በእግዚአብሔር መንግሥት ኢየሱስ ንጉሣችን ነው፡፡ እኛም ዜጎቹ ነን፤ ፈቃዱን ለማገልገል የተሰጠን የእርሱ ዜጎች ነን፡፡ የእርሱ ፍላጎጎቶች፣ ዓላማዎች፣ የልብ ናፍቆቶች እርሱ ቅድሚያ የሚሰጣቸው ጉዳዮች እና እሴቶቹ በእኛ ዘንድ ከፍ ያለ ዋጋ ያላቸውና የተመረጡ ናቸው፡፡
ቃሉ ሕጉ ነው፡፡ ስለዚህ የመንግሥቱ ሕግ ምንድነው? ዜጎቹ ምን እንዲያደርጉ ነው ኢየሱስ የሚነግራቸው?
አንተም በፍጹም ልብህ በፍጹምም ነፍስህ በፍጹምም አሳብህ በፍጹምም ኃይልህ ጌታ አምላክህን ውደድ፡፡" ኢየሱስ እንዲህ ብሏል፡- "ባልንጀራህን እንደራስህ ውደድ፡፡"
ኢየሱስ እንዲህም ብሏል፡- "የእግዚአብሔር የብሉይ ኪዳን ትእዛዛት፣ ሕግ ሁሉ እና በነቢያት የተጻፉት በሁለት ነገሮች ተጠቃለዋል። እነርሱም፡- እግዚአብሔርን መውደድ እና ሰውን መውደድ ናቸው፡፡"
ኢየሱስ ያለው ይህን ነው፡- "ደቀ መዛሙርት አድርጉ፡፡"
እርሱ አክሎ ያለውም ይህን ነው፡- "የነገርኳችሁን ሁሉ እንዲታዘዙ አስተምሯቸው፡፡"
ደቀ መዛሙርት ማድረግ የኢየሱስን ትዕዛዛት ማስተማርን የሚያጠቃልል በመሆኑ፣ አዲስ ኪዳን በአንድ ቃል ሲጠቃለል እንዲህ ሊባል ይችላል፡- "ደቀ መዛሙርት አድርጉ፡፡"
ደቀ መዝሙር እግዚአብሔርን የሚወድ እና ሰዎችን የሚወድ፣ እንዲሁም ደቀ መዛሙርትን የሚያደርግ የኢየሱስ ተከታይ ነው፡፡
**ስለዚህ ቤተ ክርስቲያን ምንድን ነች? **
ምናልባትም ቤተ ክርስቲያን ማለት ሕንጻው ነው ብላችሁ ስታስቡ ኖራችኋል፤ አንድ የሆነ የምትሄዱበት ሥፍራ አድርጋችሁም ተረድታችሁታል፡፡ የእግዚአብሔር ቃል ግን ቤተ ክርስቲያን ማለት ስብስብ እንደሆነ ይነግረናል፡፡ እናንተም እንደ ደቀ መዛሙርት አባል የሆናችሁበት የሰዎች ስብስብ ነው፡፡
"ቤተ ክርስቲያን" የሚለው ቃል በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በሦስት የተለያዩ መንገዶች ጥቅም ላይ ውሏል፡-
- ዓለም አቀፍ ቤተ ክርስቲያን … የኢየሱስ ተከታይ የሆኑ፣ የነበሩ እና ገናም የሚሆኑ ሰዎች ሁሉ አባል የሆኑበት ማለት ነው፡፡
- የከተማ ወይም የክልል ቤተ ክርስቲያን … የኢየሱስ ተከታይ የሆኑ በዓለም ላይ በአንድ በተወሰነ ሥፍራ የሚኖሩ ሰዎች ሁሉ ማለት ነው፡፡
- የቤት ቤተ ክርስቲያን … የኢየሱስ ተከታይ የሆኑ ሰዎች ሁሉ ስብስብ ሲሆን፣ ከተሰብሳቢዎቹ በአንዳቸው ወይም ከአንድ በላይ በሆኑት መኖሪያ ቤት ውስጥ የሚሰባሰቡ ናቸው፡፡
አንድ መንፈሳዊ ቤተሰብ፡- በአካባቢያቸው የሚገናኙ፣ እግዚአብሔርን የሚወዱ፣ ሰዎችን የሚወዱ እና ደቀ መዛሙርትን የሚያደርጉ እና በመጨረሻውን ዘመን ቤተ ክርስቲያንን የሚያንጹ የኢየሱስ ተከታዮች ናቸው፤ እንዲህ ያለችው ተቋም የቤት ወይም ያልተወሳሰበች - ቀላል ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡
እንዲህ ያሉት ያልተወሳሰቡ ወይም ቀላል ቤተ ክርስቲያኖች ታላቅ ነገር ለመሥራት ሲሰባሰቡ፣ የከተማ ወይም የክልል ቤተ ክርስቲያንን ይፈጥራሉ፡፡
እነዚህ ቀላል - ያልተወሳሰቡ አብያተ ክርስቲያናት በክልል ሲተሳሰሩም የታሪክን እና የሥፍራን አድማስ ተሻግረው ዓለም አቀፍ የሆነችውን ቤተ ክርስቲያን ያንጻሉ፡፡
ቀላል የቤት ቤተ ክርስቲያን ይህች ናት፡፡
**ቀላል - ያልተወሳሰቡ አብያተ ክርስቲያናት ክርስቶስ ኢየሱስን ማዕከል እና ንጉሣቸው ያደረጉ መንፈሳዊ ቤተሰቦች ናቸው፡፡ **
ቀላል - ያልተወሳሰቡ አብያተ ክርስቲያናት እግዚአብሔርን የሚወዱ፣ ሰዎችን የሚወዱ እና ደቀ መዛሙርትን የሚያፈሩ እና የሚባዙ መንፈሳዊ ቤተሰቦች ናቸው፡፡አንዳንድ አብያተ ክርስቲያናት ህንጻዎች፣ መርሃ - ግብሮች እና በጀቶች እንዲሁም ቅጥር ሠራተኞች አሏቸው፡፡ ነገር ግን፣ ቀለል ያሉ የቤት ቤተ ክርስቲያናት እግዚአብሔርን ለመውደድ፣ ሰዎችን ለመውደድ እና ራሳቸውን የሚያባዙ ደቀ መዛሙርትን ለማባዛት ከላይ ከተጠቀሱት ነገሮች ውስጥ ምንም አያስፈልጋቸውም፡፡ ማንኛውም ተጨማሪ ነገር ቤተ ክርስቲያንን የበለጠ የሚያወሳስባት እና ለመባዛቷ እንቅፋት የሚሆን በመሆኑ፣ ሥልጠናችን ውስጥ እንደ ቤተ ክርስቲያን ሕንጻዎች፣ እንደ ቤተ ክስቲያን መርሃ-ግብሮች እና እንደ በጀት እንዲሁም እንደ ቅጥር ሠራተኞች ያሉትን ጉዳዮች በመባዛት መርህ ለታነጹት ለከተማ እና ለክልል አብያተ ክርስቲያናት እንተዋቸዋለን፡፡
ልብ አድርጉ፣ "ዙሜ" ማለት "እርሾ" ማለት ነው፤ ይህም ቅንጣት የሆነ አንድ የሴል ሕዋስ ሲሆን፣ ራሱን ግን በፍጥነት የሚያባዛ ወይም የሚያራባ ነው፡፡
በዙሜ ሥልጠና እኛም ልክ እንደዚያ እርሾው ቀላል እና የምንባዛ እንሆናለን፡፡ ከመባዛታችን አስቀድመን ግን እግዚአብሔር እንዲባዛ የሚፈልግው ምን እንደሆነ ስለማወቃችን እርግጠኛ እንሁን፡፡ ምክንያቱም መባዛት መልካም ነገር ቢሆንም፣ ሁልጊዜ ግን መልካም ላይሆን ይችላል፡፡የካንሠር ሕመም የብዜት ውጤት ነው፡፡ ሆኖም ግን ገዳይ ነው፡፡ስለዚህ ሞትን ሳይሆን ሕይወትን የምናባዛው እንዴት ነው? ደቀ መዛሙርትን ማባዛት የተገባን ወይም ለዚህ የበቃን ደቀ መዛሙርት መሆናችንንስ እንዴት ማረጋገጥ እንችላለን?
ተወያዩ
(10 min)
- ስለ ቤተ ክርስቲያን ስታስቡ ወደ አእምሮአችሁ የሚመጣው ምንድን ነው?
- በዚያ ስዕል እና በቪዲዮው ላይ እንደ ‹‹ቀላል ቤተ ክርስቲያን›› በተገለጸው መካከል ያለው ልዩነት ምንድን ነው?
- የትኛውን ማባዛት ቀላል ነው ብላችሁ ታስባላችሁ እና ምክኒያታችሁስ?
READ
(5 min)
እግዚአብሔርን መስማትና መታዘዝ
እንኳን ወደ ዙሜ ሥልጠና እንደገና በሰላም መጣችሁ፡፡ በዚህ ክፍለ-ጊዜ ከእግዚአብሔር ስለመስማት እና ለሰማነው ስለመታዘዝ እንማራለን፡፡ እስትንፋስ ሕይወት ነው፡፡ ዓየር ወደ ውስጥ እንስባለን፡፡ ወደ ውጪም እንተነፍሳለን፡፡ ሕይወት እንተነፍሳለን ማለት ነው፡ መተንፈስ በእግዚአብሔር መንግሥት ውስጥ ያን ያክል በጣም አስፈላጊው ነገር ነው፡፡ በእርግጥ እግዚአብሔር ቅዱስ መንፈሱን "እስትንፋስ" ብሎ ይጠራዋል፡፡ በእግዚአብሔር መንግሥት ውስጥ ከእግዚአብሔር ስንሰማ ዓየር ወደ ውስጥ ሳብን ማለት ነው፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ አማካኝነት ከእግዚአብሔር ስንሰማ ዓየር ወደ ውስጥ ሳብን ማለት ነው፡፡ በጸሎት ከእግዚአብሔር ስንሰማ እና ከእርሱ ጋር ስንነጋገርም እንዲሁ ዓየር ወደ ውስጥ ሳብን ማለት ነው፡፡ በአካሉ፤ በቤተ ክርስቲያን ወይም በሌሎች የኢየሱስ ተከታዮች በኩልም የእግዚብሔርን ቃል ስንሰማ ዓየር ወደ ውስጥ ሳብን ማለት ነው፡፡ በሥራዎቹ በኩል እርሱን ስንሰማ፤ ማለትም በሁነቶች፣ በልምዶች እንዲሁም አንዳንድ ጊዜ ልጆቹ በስደት እና በስቃይ ውስጥ እንዲያልፉ ሲፈቅድም፣ በዚያ ውስጥ እርሱን ስንሰማም፣ ዓየር ወደ ውስጥ ሳብን ማለት ነው፡፡ በእግዚአብሔር መንግሥት ውስጥ ከእግዚአብሔር የሰማነውን ወደ ተግባር ስንለውጥም መተንፈሳችን ነው፤ ስንታዘዝም እንዲሁ ወደ ውጪ መተንፈሳችን ነው፡፡ ወደ ውጪ መተንፈስ መታዘዝ፣ ለመታዘዝ ወደ ውጪ መተንፈስ - መታዘዝ፡፡ ለመታዘዝ ወደ ውጪ መተንፈስ ማለት አስተሳሰባችንን፣ የአፋችንን ቃል እና ተግባራችንን በመለወጥ ከኢየሱስ እና ከፈቃዱ ጋር እንዲጣመር ማድረግ ማለት ነው፡፡ አንዳንድ ጊዜ በመታዘዝ ወደ ውጪ መተንፈስ ማለት ኢየሱስ ለእኛ ያካፈለውን፣ የሰጠንን በመስጠት እግዚአብሔር እኛን እንደባረከን ሌሎችም እንዲባረኩ ማድረግ ማለት ነው፡፡ ለአንድ የኢየሱስ ተከታይ ይህ ዓየርን ወደ ውስጥ መሳብ እና ወደ ውጪ መተንፈስ አንገብጋቢ ጉደይ ነው፡፡ የሕይወቱም መሠረት ነው፡፡ "ኢየሱስ መለሰ እንዲህም አላቸው፦ እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ አብ ሲያደርግ ያየውን ነው እንጂ ወልድ ከራሱ ሊያደርግ ምንም አይችልም፤ ያ የሚያደርገውን ሁሉ ወልድ ደግሞ ይህን እንዲሁ ያደርጋልና።" "እኔ ከራሴ አልተናገርሁምና፤ ነገር ግን የላከኝ አብ እርሱ የምለውን የምናገረውንም ትእዛዝ ሰጠኝ።" ኢየሱስ እንዳለው የተናገረውን እና ያደረገውን እያንዳንዱን ነገር ለማከናወን መሠረት ያደረገው ከእግዚአብሔር በመስማት እና ያዳመጠውን ለመተግበር በመታዘዝ ነው፡፡ ዓየርን ወደ ውስጥ መሳብ፡- እግዚአብሔርን ማዳመጥ ነው፡፡ ዓየርን ወደ ውጪ መተንፈስ፡- አንድ ሰው ከእግዚአብሔር ለሰማው ነገር መታዘዝ እና የሰማውንም ለሌሎች ማካፈል ነው፡፡ ኢየሱስ እንዳለው ተከታዮቹ በመንፈስ ቅዱስ - በእያንዳንዳችን እርሱን በምንከተው ሁሉ ላይ እፍ ባለው - በእስትንፋሱ ምክንያት ከእግዚአብሔርን እንሰማለን፡፡ ኢየሱስ እንዲህ ብሏል፡- "አብ በስሜ የሚልከው ግን መንፈስ ቅዱስ የሆነው አጽናኝ እርሱ ሁሉን ያስተምራችኋል እኔም የነገርኋችሁን ሁሉ ያሳስባችኋል::" ዓየርን ወደ ውስጥ መሳብ፡- እግዚአብሔርን ማዳመጥ ነው፡፡ ዓየርን ወደ ውጪ መተንፈስ፡- አንድ ሰው ከእግዚአብሔር ለሰማው ነገር መታዘዝ እና የሰማውንም ለሌሎች ማካፈል ነው፡፡ ይህንን ሲል ኢየሱስ እንዴት መኖር እንዳለብን እያመላከተን ነው፡፡ ስለዚህ የእግዚአብሔርን ድምጽ የምንሰማው እንዴት ነው? የምንታዘዘውንስ ነገር የምናውቀው እንዴት ነው? ኢየሱስ "መልካም እረኛ እኔ ነኝ" ብሏል፡፡ ተከታዮቹን ደግሞ "በጎቼ" ብሏቸዋል፡፡ ኢየሱስ እንዲህም ብሏል፡- በጎቼ ድምጼን ይሰማሉ፤ እኔም አውቃቸዋለሁ፤ እነርሱም ይከተሉኛል፡፡ ኢየሱስ እንዳለውም የእግዚአብሔር የሆነ ሁሉ እግዚአብሔር የሚለውን ይሰማል፡፡ እናንተ የማትሰሙበት ምክንያት የእግዚአብሔር ስላልሆናችሁ ነው፡፡ እንደ ኢየሱስ ተከታይ፣ ድምጹን ለመስማት ራሳችንን መስጠት - መቁረጥ አለብን፡፡ የእርሱን ድምጽ የምንሰማው በጥሞና - ባለመናወጥ - በእርጋታ ሆነን ነው፡፡ የእርሱን ድምጽ የምንሰማው ኢየሱስ ላይ በማተኮር ነው፡፡ የእርሱን ድምጽ የምንሰማው በሃሳባችን፣ በራዕያችን፣ በስሜታችን እና በምናባችን ነው፡፡ የእርሱን ድምጽ በትክክል የምንሰማው ስንጽፈው እና የሰማነውንም ስንመረምረው ነው፡፡ የሰማነው ሁሉ፣ ያሰብነው ሁሉ፣ በራዕያችን የታየን ሁሉ፣ የተሰማንም ሁሉ ወይ በምናባችን የተከሰተልን ሁሉ ግን የእግዚአብሔር ድምጽ ነው ማለት አይደለም፡፡ አንዳንድ ጊዜ የእግዚአብሔርን ድምጽ መሳይ የጠላት ድምጽም ይመጣል፡፡ ኢየሱስ እንዳለው ጠላታችን ውሸታም ነው፡፡ ኢየሱስ እንዳለውም ጠላታችን የሚመጣው ሊሰርቅ፣ ሊገድል እና ሊያጠፋ ነው፡፡ ነገር ግን እግዚአብሄር ከእርሱ እንደምንሰማ እና ሲናገርም እርሱ እንደሆነ እናውቃለን። በልምምድ እና በጸሎት የእርሱን ድምጽ እንደሚገባው ማወቅ እንችላለን፡፡ የምንሰማው ድምጽ ከእግዚአብሔር ይሁን ወይም ከሌላ መረዳት እንችላለን፡፡ ከዚህ ቀጥሎ የተመለከቱት የምንሰማውን ድምጽ ለመመርመር የሚረዱ የተወሰኑ መንገዶች ናቸው፡- ኢየሱስ ሲናገር፣ ድምጹ ሁልጊዜም ከተጻፈው የእግዚአብሔር ቃል ወይም ከመጽሐፍ ቅዱስ ጋር በሚጣጣም መንገድ ነው፤ መጽሐፍ ቅዱስ ቀድሞ በነገረን መንገድ ነው፡፡ በድምጽ የምንሰማው ቃሉ ከተጻፈው ቃል ጋር በፍጹም አይጣረስም፤ አይምታታምም፡፡ ኢየሱስ ሲናገር፣ ድምጹ ልባችንን በተስፋ እና በሰላም ይሞላዋል፡፡ ድምጹ በኩነኔ እና በተስፋ መቁረጥ ስሜት ውስጥ አይተወንም፡፡ ኢየሱስ ማንንም አይኮንንም፡፡ ከዚያ ይልቅ በፍቅር ያቀናናል፡፡ የኢየሱስ ድምጽ የሥጋን ሥራዎች፣ ወሲባዊ ኢ-ሥነምግባርን፣ የምንዝርናን፣ ቅድስና የለሽ ሃሳብን፣ ጣዖትን ማምለክን፣ ጥንቆላን፣ ጥላቻን እና ጸብን፣ ቅናት እና መራር ቁጣን፣ ራስ ወዳድነትን፣ አመጸኛ ተቃዋሚነትን፣ ክፍፍልን፣ ምቀኝነትን፣ ሥካርን እና ዘፋኝነትን በሰው ልብ ውስጥ አያነሳሳም፡፡ የእነዚህ ነገሮች ነገሮች መነሳሻ የእግዚአብሔር ድምጽ አይደለም፡፡ ኢየሱስ ሲናገር፣ የኢየሱስ ድምጽ የመንፈስ ቅዱስን ፍሬዎች ያፈራል፡፡ ፍቅርና ሃሴትን፣ ሰላምና ትዕግስትን፣ ርህራሄና ደግነትን፣ ታማኝነትን፣ ጨዋነትን እና ራስን መግዛትን ይሰጠናል፡፡ ኢየሱስ ሲናገር ድምጹ በጥርጥር ፋንታ መተማመንን ይሞላናል፡፡ በመጨረሻም፣ በውስጣችንም ከእግዚአብሔር የመስማትን ልምድ እና የድምጹን ሰላም እናውቃለን፡፡ ሁሉንም ነገር በአንድ ጊዜ ላንሰማ እንችላለን፡፡ ከድምጹ በመጨረሻ ማወቅ የሚገባንን የሚያሳውቀንን ያክል ብቻ ልንሰማ እንችላለን፡፡ የምንሰማው ግን ነገር ግን የጸና እና የማይቀለበስ ወይም የማይለወጥ ነው፡፡ ለኢየሱስ ተከታይ ሁሉ ታዲያ የምሥራቹ ይህ ነው፡- ከእግዚአብሔር ዘንድ ወደ ውስጥ ዓየር ስንስብ፣ ዓየርን ወደ ውጪ ስንተነፍስ እና ለእግዚአብሔር በመታዘዝ የሰማነውን ለሌሎች ስናካፍል፣ እግዚአብሔር ከቀደመውም የበለጠ በግልጽ ይናገረናል፡፡ የእስትንፋሱን እፍታ ከቀደመውም በበለጠ በእኛ በኩል እንዲያልፍ ያደርጋል፡፡ ድምጹንም የበለጠ ግልጽ በሆነ መንገድ እንሰማዋለን፡፡ የእርሱንም ድምጹ በሚገባ እናውቀዋለን፤ የሌላውን ድምጽ ግን አይደለም፡፡ ሥራውንም በዓለም ላይ እናየዋለን፤ ራሳችንንም በሥራው ተሳታፊ እናደርጋለን፡፡ ዓየር ወደ ውስጥ እንስባለን፡፡ ወደ ውጪም እንተነፍሳለን፡፡ ይህም ሕይወት ነው፡፡
ተወያዩ
(10 min)
- የእግዚአብሔርን ድምጽ መስማትና ማወቅ መማሩ አስፈላጊ የሆነው ለምንድነው?
- ከጌታን መስማት እና ምላሽ መስጠት በእርግጥ ልክ እንደመተንፈስ ነውን? ለምን ወይም ለምንስ አይሆንም?
ይከልሱ
(1 min)
በዚህ ክፍለ ጊዜ የተሰሙ ጽንሰ-ሐሳቦች፡-
- እግዚአብሔር ተራ ሰዎችን ይጠቀማል
- የደቀ መዝሙር እና የቤተክርስቲያን ቀለል ያለ ፍቺ
- መንፈሳዊ መተንፈስ እግዚአብሔርን መስማት እና መታዘዝ ነው።
NEXT STEP
ታዘዙ
እነዚህን ትርጓሜዎች ከጓደኛቻችሁ ጋር መጋራት ተለማመዱ እና ጌታ በልባችሁ እና በነፍሳችሁ ውስጥ እንዲሰርጽባችሁ ጸልዩ። ከማን ጋር እንድትካፈሉ እንደሚፈልግ ጌታን ጠይቁ።
አካፍሉ
ፍቺዎቹን እንድታደርጉ ጌታ ለሚያሳስባችሁ ማንኛውም ሰው አካፍሉ። ከዚያ ለሌላ ሰው ማካፈል እንዲችሉ አስታጥቁዋቸው።
